የአየር ጤና 2ኛ ደረጃ ት/ቤት ተማሪዎች በልደታ ማኑፋክቸሪንግ ኮሌጅ ትምህርታዊ ጉብኝት አደረጉ
ጥቅምት 3 ቀን 2018 ዓ.ም
በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ የሚገኘው የአየር ጤና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች በልደታ ማኑፋክቸሪንግ ኮሌጅ በመገኘት በኮሌጁ የሚሰጡትን የተለያዩ የሙያ ስልጠና ዘርፎች የተመለከቱበትን ትምህርታዊ ጉብኝት አካሄዱ።
የጉብኝቱ ዋነኛ አላማ ተማሪዎቹ በኮሌጁ የሚሰጠውን የተግባር ስልጠና በመመልከት ለቀጣይ የሙያ ምርጫቸው የተሻለ ግንዛቤ እንዲያገኙ ማስቻል መሆኑ ተገልጿል።
በቆይታቸው ወቅት ተማሪዎቹ በኮሌጁ ውስጥ የሚገኙትን የተለያዩ የስልጠና ወርክሾፖችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በዚህም መሰረት በኮንስትራክሽን፣ በጋርመንት (ልብስ ስፌት)፣ በሆቴል (ምግብ ዝግጅት)፣ በእንጨት ሥራ፣ በቆዳ ማቀነባበሪያ (ሌዘር)፣ በኢንፎርሜሽን ኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT)፣ በብረታ ብረት ሥራ እና በአውቶሞቲቭ ቴክኖሎጂ የትምህርት ክፍሎች በመገኘት የሥልጠና አሰጣጥ ሂደቱን ተመልክተዋል።
ተማሪዎቹ በጉብኝቱ ወቅት በተሰጣቸው ማብራሪያ እና ባዩት የተግባር ስራ እንቅስቃሴ መደሰታቸውን ገልጸው፣ ጉብኝቱ ለወደፊት የስራ መስክ ምርጫቸው አጋዥ መሆኑን ተናግረዋል።
ኮሌጁ ለ2018 ዓ.ም. የቅበላ አቅሙን ለማሳደግ የጀመረውን የማህበረሰብ ግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
በቀጣይም ድላችን 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የሚገኙ ተማሪዎችን እና መምህራንን በማሳተፍ ተመሳሳይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች እንደሚሰሩ ታውቋል።


.